ያልተጠየቀ ዳኝነት አይሰጥም፤ በግልጽ ያልተሰጠ ፍርድም አይፈጸምም።
መሰረታዊው የፍትሐብሔር ክርክር አመራር መርህ በግልጽ ያልተጠየቀ ዳኝነት አይሰጥም የሚል ነው። ይህም ስለፍርድ በሚያትተው የፍትሀብሄር ሥነ-ሥርዓት ህጉ ክፍል በቁጥር 182/2/ ስር በግልጽ ተደንግጓል። ፍርድና ውሳኔ በዚህ መርህ መሰረት በጥብቅ ሥርዓት ከተሰጠ በኋላ ፍርድ አስፈጻሚው እንደፈለገው ከፍርዱ ይዘት እየወጣ የሚወስንና የሚያስፈጽም ከሆነ ያልተጠየቀ ዳኝነት እንደመስጠት የሚቆጠር በመሆኑ ይህን መርህ የሚቃረን ነው።
የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በኢፌዴሪ ህገ-መንግስት አንቀጽ 80/3/ሀ በተሰጠው ስልጣን መሰረት የሚሰጣቸው ውሳኔዎች በየትኛውም ደረጃ የሚገኙ ፍርድ ቤቶችን የሚያስገድዱ ናቸው። ችሎቱ በሰ/መቁጥር 152172 (ቅጽ 23)፥ 29949 (ቅጽ 6)፥ 103787 (ቅጽ 19)፥ 28019 እና 29344 (ቅጽ 7)፥ 50148 (ቅጽ 9)፥ 96814 (ቅጽ 18) እና በሌሎችም መዛግብት በተሰጡ የህግ ትርጉሞች አንድ ሰው በአፈጻጸም ሊገደድ የሚችለው በህግ አግባብ የተፈረደ ፍርድ ሲኖር ብቻ ስለመሆኑ፤ ግልጽ ፍርድ ያላረፈበት ጉዳይ ሊፈጸም እንደማይችል፤ አፈጻጸም ችሎቶች ስለፍርድ አፈጻጸም የተዘረጉትን ሥርዓቶች በመከተል እንደፍርዱ ከማስፈጸም በቀር የአንድን ፍርድ ይዘት አድማስ ማጥበብም ሆነ ማስፋት እንደማይችሉ፤ አንድ የፍርድ አፈጻጸም ክስ ማመልከቻ ይፈጸም የተባለውን ፍርድ ብቻ መሰረት ያደረገ ሊሆን እንደሚገባ አሰገዳጅ ትርጉም ሰጥቷል።
ያልተጠየቀ ዳኝነት አይሰጥም፥ ያልተሰጠ ፍርድ አይፈጸምም የሚለው መሪ ህግ የፍትሀብሄር ሥነ-ሥርዓት ህግ ዋነኛ መርህ የሆነውም ህገ-መንግስታዊ የሆኑ እና በዓለም አቀፍ የሰብዐዊ መብት የቃል ኪዳን ሰነዶች የተረጋገጡ መሰረታዊ እና ሥነ-ሥርዓታዊ መብቶችን/Substantive and Procedural Rights/ ለማክበር እና ለማስከበር ነው። ተከሳሾች የሚቀርብባቸውን ማናቸውንም ክስ አስቀድመው የማወቅ፥ የመቃወም፥ የመከራከር፥ የመደመጥና ለጉዳዩ አግባብነት ያላቸውን ማስረጃዎች አቅርበው የማስተባበልና ፍትህ የማግኘት መብት እንዳላቸው (የሥነ-ሥርዓት መብቶች-Due Process Rights) በኢፌዴሪ ህገ-መንግስት አንቀጽ 20 እና 37 እንዲሁም በዓለም አቀፍ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ቃል ኪዳን አንቀጽ 14 ተደንግጓል። የህገመንግሰቱ አንቀጽ 40 ም የአንድ ሰው ንብረት ተገቢውን የሥነ-ሥርዓት ሂደት ሳይከተል ሊወሰድበት/ሊተላለፍ እንደማይችል የሚያዝዝ ነው።
ጠበቃ እና የህግ አማካሪ እንዳላማው አለልኝ/0912771896/